
ስለ ቤተክርስቲያናችን
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን: አህጽሮት–ጽሑፍ
ኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ ከአምልኮተ ባዕድ ሸሽታ አምልኮተ እግዚአብሔርን ስትፈጽም የኖረች ቅድስት ሀገር ናት። በኋላም በዘመነ ድኅረ ልደተ ክርስቶስ በሐዋርያት ሥራ ምዕ.8 ላይ እንደሰፈረው በክርስትና ሃይማኖት አምነው ከተጠመቁት የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች መካከል ኢትዮጵያውያን ይገኙበታል። የታሪክ ድርሳናት አንደሚጠቁሙትም ሃገራችን ኢትዮጵያ የክርስትና ሃይማኖትን የግዛቷ (የመንግስቷ) ሃይማኖት በማድረግ ያወጀችና የተገበረች የመጀመሪያዋ ሃገር ናት። በመሆኑም ክርስትና በ4ኛው ክፍለ ዘመን በአብርሃና አጽብሐ ዘመነ መንግስት 298-336 ዓ.ም ባሉት ጊዜያት ውስጥ የሃገራችን ዋና እምነት ሲሆን አቡነ ሰላማ (ከሣቴ ብርሃን) በ330 ዓ.ም የመጀመሪያው ጳጳስ ሆነው ተሹመዋል።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ልዩ የሚያደርጋት ብሉይ ኪዳንና አዲስ ኪዳንን አናባ፣አዋህዳ፣ አስተባብራ የያዘች ብቸኛው ቤተክርስቲያን በመሆኗ ነው። ይህም የሆነበት ምክንያት በመጽሐፈ ነገሥት ቀዳማዊና በዜና መዋዕል ካልዕ እንደተገለጸው ንግሥተ ማክዳ ወደ ቅድስት ሃገር እየሩሳሌም ደርሳ ወደ ሃገሯ ከተመለሰች በኋላ ኢትዮጵያ በህገ ኦሪት አማካኝነት አምልኮተ እግዚአብሔርን እንድትፈጽም አድርጋለች፤ ሥርዓተ ኦሪትም እስክ ልደተ ክርስቶስ ጸንቶ ነበርና ክርስትና ወደ ኢትዮጵያ ሲዘልቅ፤ ኢትዮጵያውያን በህገ ኦሪት እግዚአብሔርን ያመልኩ ስለነበር አዲሱን ክርስትናን ሲቀበሉ የቀደመውን ኦሪትን ሙሉ በሙሉ በመጣል ሳይሆን ከወንጌል ጋር በማጣጣም፣ በማስተባበር ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ከጥንት ጀምሮ የቆየው የኢትዮጵያና የእስራኤል በተለይ ደግሞ ከቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ጋር የነበረው ግንኙነት ተጽዕኖ እንዳሳደረ የታሪክ ማስረጃዎች ያወሳሉ።
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ‘ተዋሕዶ’ የሚለው ቃል ወሳኝነቱ ጎልቶ ሲገኝ ትርጉሙም “አንድ ሆኖ” ለማለት ነው። ቃሉም የክርስቶስን አንድ ባሕርይነት ለማጠየቅ ያቀፈውን ጽኑ እምነት ለመግለጽ ገዥ ቃል ሁኖ እናገኘዋለን። በመሆኑም የኢኦተቤ ከኦሬንታል(ከምስራቅ አብያተ ክርስትያንት መካካል አንዷ ስትሆን የኬልቄዶን ጉባኤ ድንጋጌዎችን ባለመቀበል፣ የክርስቶስ አንድ ባሕርይን ወይም የስጋና መለኮትን መዋህድ ታጸናለች።
የኢኦተቤ ባህልና ትውፊት ምስጢራተ ቤተክርስቲያንና የቅድሴ አገልግሎት ጥንታዊ በሆነው የግዕዝ ቋንቋ ሲከናወን የቆየ ሲሆን፤ የሕዝበ ክርስትያኑ ቁጥር እየጨመረ ስለመጣ የቅዳሴና ሌሎች አገልግሎቶች ወደተለያዩ ቋንቋዎች ማለትም ወደ አማርኛ፣ ኦሮምኛ፣ አረብኛ እና እንግሊዚኛ ተተርጉመዋል።
የኢኦተቤ በማህበረሰቡ ህይወት ለዘመናት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረገችና እያደረገች ያለች ቤተክርስቲያን ናት። መንበሯም፤ መንበረ ተክለሃይማኖት በሃገሪቱ መዲና አዲስ አበባ ሲገኝ፣ ከ45 ሚሊዮን በላይ ክርስቲያን ተከታዮች አሏት። የክርስቲያኖች ቁጥርም ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ ሰለመጣ በኢኦተቤ የሚተዳደሩ አብያተ ክርስቲያናት በመላው ዓለም ተሰራጭተው ይገኛሉ።
ስለሆነም ይህ የሜልበርን ደብረ ገነት ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን በኢኦተቤ አስተዳደር ስር የሚገኝ ደብር ሆኖ፤ በኢኦተቤ ዶግማ፣ ቀኖና እና ትውፊት መሠረት ወንጌልን ይሰብካል።
የሜልበርን ደብረ ገነት ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስትያን ወደ ቤተ እግዚአብሔር እንገሰግስ ዘንድ ከመጋበዙም በላይ፤ በአገልግሎትም የድርሻችንን እንወጣ ዘንድ ጥሪውን ያስተላልፋል።
ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን!
አሜን
