ከተራ ማለት ምን ማለት ነው?

ከተራ ማለት ምን ማለት ነው?

አቅራቢ  መጋቢ ጥበብ ኤርሚያስ ባዬ

በየዓመቱ የጥምቀት በዓል በድመቀት ይከበራል፡፡ ከበዓሉ በፊት የከተራ በዓል የሚከበርበትን ታሪካዊና ሃይማኖታዊ ገለጻ ከተራ ከበበ ካለው የግእዝ ግሥ የወጣ ነው፡፡ ፍችው ውኃ መከተር፣ መገደብ ማለት ነው፡፡ የጥምቀት ዋዜማ ታቦተ ሕጉ ከቤተ መቅደስ ወጥቶ ውኃ ባለበት አካባቢ ስለሚያድር የየአጥቢያው ሕዝብ እየተሰበሰበ በወንዝ ዳር ወይም በምንጭ አካባቢ ድንኳን ይተከላል፡፡ ድንኳንም ከሌለ ዳስ ሲጥል ይውላል፡፡ የምንጮች ውኃ ደካማ በመሆኑ እንዲጠራቀም ይከተራል ጉድጓድ እየተቆፈረ ውኃው እንዳይሄድ ይገደባል፡፡ ketera 2 2“ከተራ” በመባል የሚታወቀው- ዋዜማው” ሠርግው /1981፣8/ እንደገለጹት “ከተራ” የሚለው ቃል “ከተረከበበ ካለው የግዕዝ ግስ የወጣ ነው፡፡ ከተራ ፍቺውም ውኃ መከተር፣ ወይም መገደብ ማለት ነው፡፡” ብለው ሲፈቱ፣ ደስታ ተከለ ወልድ /1962፣ 694/ ደግሞ የጥምቀት ዋዜማ፣ ጥር 10 የጠራ ወራጅ ውኃ የሚከተርበት ታቦትና ሰው ወደ ዠማ ወንዝ የሚወርዱበት ጊዜ” ነው በማለት ይፈቱታል፡፡

ኪዳነ ወልድ ክፍሌም /1948፣ 555/ ከተረ የሚለውን ቃል በቁሙ፣ “ዘጋ፣ አቆመ፣ አገደ፣ ከለከለ፡፡” ማለት ነው ብለው ይፈቱታል፡፡ በየዓመቱ ጥር 10 ቀን የምእመናኑ አብዛኛው ሥራ ውኃውን መከተርና መገደብ በመሆኑ ዕለቱ ከተራ የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ ውኃው የሚከተረው በማግሥቱ ጥር 11 ቀን የጥምቀት በዓል ስለሚከበር ለሕዝቡ መጠመቂያ እንዲሆን ነው፡፡ በየሰበካው ቦታ ተለይቶና ተከልሎ ታቦታቱ በዳስ ወይም በድንኳን የሚያድሩበት፣ የተለያዩ የውኃ አካላት ተጠርገው የሚከተሩበት ወይም ሰው ሠራሽ የግድብ ውኃ የሚበጅበት ስፍራ ‹‹ባሕረ ጥምቀት››፣‹‹የታቦት ማደርያ›› እየተባለ ይጠራል፡ ባሕር፡- የውኃ መሰብሰቢያ (ምእላደ ማይ፣ የውኃ መከማቻ (ምቋመ ማይ) ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ‹‹የውኃ አገር›› /መካነ ማይ፣ዓለመ ማይ/ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በቅዱስ ላልይበላ ዘመነ መንግሥት በኢትዮጵያ ምድር እየተመላለሱ በብሕትውና እና በስብከተ ወንጌል ያገለግሉ የነበሩት ጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በአክሱም፣ በመቐለና በመርጡለ ማርያም እየተዘዋወሩ ባሕረ ጥምቀቱን ባርከዋል፡፡ በዐፄ ይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት (1260-1275 ዓ.ም) በጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት (1203-1204 ዓ.ም) አሳሳቢነት የተጀመረው ሥርዐተ በዓል ተጠናክሮ እንዲቀጥል በዐዋጅ ትእዛዝ አስተላልፈዋል፡፡

ታቦታቱም በሕዝብ ጥበቃና ክብካቤ ተደርጎላቸው በየጥምቀተ ባሕሩ እንዲያድሩ ወስነዋል፡፡ የበዓሉ አከባበር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየሰፋና አድማሱ ብሔራዊነትን እየያዘ መጣ፡፡ ከዐፄ ገብረ መስቀል ጀምሮ የአደባባይ በዓል የሆነው የጥምቀት በዓል በ15ኛው ክ/ዘመን በደገኛው ኢትዮጵያዊው ንጉሠ ነገሥት ዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ(1426-1460 ዓ.ም) አማካኝነት ታቦታቱ ወደ ወንዝ ወርደው ዕለቱን እንዳይመለሱ፣ በዚያ ፈንታ በጥምቀት ዋዜማ ጥር 10 ቀን ከሰዓት በኋላ ወደ ባሕረ ጥምቀቱ ወርደው እንዲያድሩ፣ አገሩን በኪደተ እግር ይባርኩም ዘንድ በሄዱበት መንገድ እንዳይመለሱ በዐዋጅ ወሰኑ፡፡ ይህን ታሪክ በመከተል ዐፄ ናዖድ (1486-1500) ዓ.ም) ማንኛውም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ምእመን ታቦተ ሕጉ ወደ ባሕረ ጥምቀቱ በሚወርድበት እና ከባሕረ ጥምቀቱ ወደ ቤተ መቅደሱ በሚመለስበት ጊዜ አጅቦ አውርዶ፣ አጅቦ መመለስ እንዳለበት በዐዋጅ አስነግረው ነበር፡፡ ሕዝቡም ታቦታተ ሕጉን በሆታና በእልልታ ከቤተ መቅደስ አጅቦ ከአወጣ በኋላ በባሕረ ጥምቀት ከትሞ ማደር ጀመረ ።/ ሐመር ጥር/የካቲት 1998 ዓ.ም/ ketera 3ታቦታት ከአንድ በላይ ሆነው ወደ ከተራው ስለሚሄዱ እግዚአብሔር አምላክ ለነብዩ ሙሴ “የታቦት መኖር ከእናንተ ጋር የመኖሬ ምልክት ነው” ዘፀ 25÷1 እንዳለው ታቦተ ሕጉን ተሸክመው ዮርዳኖስን እንደ ተሻገሩት ካህናተ ኦሪት፤ ካህናቱ የማይለወጠውን ታቦተ ሕጉን በራሳቸው ተሸክመው የብሉዩን ሥርዓት ከሐዲስ ኪዳን ጋር አንድ አድርገው የሐዲስ ኪዳን መሠረት ኢየሱስ ክርስቶስን እያሰቡ፤ ካህናተ ሐዲስም ወደ ከተራ (ዮርዳኖስ) ይጓዛሉ፡፡

ሊቃውንቱም እንዲሁ ለበዓሉ የሚስማማውን ቃለ እግዚአብሔር እያደረሱ እንደሚያድሩ ሊቀ ጠበብት ሐረገወይን አገዘ ያስረዳሉ። ሊቀ ጠበብት አያይዘውም የከተራ ዕለት ጥር 10 ቀን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ እጅ ለመጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ የሄደበትን ለማዘከር ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ኃዳፌ ነፍስ ለጻድቃን የሚለውን ዋዜማ ይቆማሉ፡፡ የዋዜማው ቀለም ከቀኑ በአራት ሰዓት በመላው አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ይጀመራል ከዚያም የዋዜማው ሥርዐት ቅዱስ ተብሎ እስከ ሰላም ያለው ቀለም ይደርሳል፡፡ በዕለቱም ቅዳሴ ይቀደሳል፡፡ ታቦተ ሕጉን የሚያነሡት ሰሞነኛ ካህን ከምግበ ሥጋ ተከልክለው ለዕለቱ የሚገባውን ጸሎት ያደርሳሉ፡፡ በከተራው ዕለት ድንኳን ተተክሎ፣ ዳሱ ተጥሎና ውኃው ተከትሮ ሁሉም ነገር ከተስተካከለ በኋላ ታቦተ ሕጉ የሚንቀሳቀስበት ሰዓት ሲደርስ የየቤተ መቅደሱ ታቦታት በወርቅና በብር መጎናጸፊያ እየተሸፈኑ በተለያየ ኅብር በተሸለሙ የክህነት አልባሳት በደመቁ ካህናትና የመጾር መስቀል በያዙ ዲያቆናት ከብረው፣ ከቤተ መቅደስ ወደ አብሕርት / ምጥማቃት/ ለመሄድ ሲነሡ መላው አብያተ ክርስቲያናት የደወል ድምፅ ያሰማሉ፡፡ ምእመናን ከልጅ እስከ ዐዋቂ በዐጸደ ቤተ ክርስቲንና ታቦታቱ በሚያልፉባቸው መንገዶች ‘’ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ …’’ እንደሚባለው ያማረ ልብሳቸውን ለብሰው በዓሉን ያደምቃሉ፡፡ ሊቀ ጠበብት የበዓሉን ሂደት ሲገልጹ ታቦቱ ከመንበረ ክብሩ ሲነœ ‹‹ዮም ፍስሀ ኮነ››ተብሎ ከተጸነጸለ በኋላ ታቦቱ ወጥቶ ወረደ ወልድ እምሰማያት ውስተ ምጥማቃት የሚለው ሰላም በሊቃውንቱ ይዘመራል፣ ይጸነጸላል፣ ይመላለሳል፡፡

የወርቅ ካባና ላንቃ የለበሱ ቀሳውስት፣ መነኮሳት ጥላ የያዙት ከታቦቱ ጎን መስቀልና ጽና የያዙት ከታቦቱ ፊት ይሄዳሉ፡፡ እንደ ቀሳውስቱ ተመሳሳይ ልብሰ ተክህኖ የለበሱት ዲያቆናት ጥላ፣ መስቀልና ቃጭል ይዘው እያቃጨሉ ከቀሳውስቱ ፊት በመሆን ያጅቧቸዋል፡፡ ከነዚህም ሌላ ካባ፣ ላንቃ ጥንግ ድርብ የለበሱ መዘምራን የብር፣ የነሐስ መቋሚያና ጸናጽል ይዘው ‹‹ወረደ ወልድ›› የሚለውን አመላለስ እያሸበሸቡ ዲያቆናቱን ቀድመው ይሄዳሉ፡፡ የደብር አለቆችና አበው ካህናት ታቦቱን ተከትለው ይጓዛሉ፡፡ የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎችም በተለያዩ ቀለማት ባሸበረቁ አልባሳት ተውበው ትርዒት እያሳዩ “ወረደ ወልድ፣ እግዚኡ መርሐ፣ ሆረ ኢየሱስ” እና ሌሎችንም የአማርኛ መዝሙራትን እየዘመሩ፣ እናቶች “ነይ ነይ እምዬ ማርያም” እያሉ ሌሎችም ምስጋናዎችም እየቀረቡ ጉዞ በዝግታ ወደ ጥምቀተ ባሕር ይሆናል፡፡የከተራ በዓል ማክበሪያ ቦታ እንደደረሱ ታቦታቱ በድንኳኑ አጠገብ ቆመው ‹‹ወረደወልድ›› የሚለው ሰላም ተመርቶ በአግባቡከተለዘበ በኋላ ጸሎት ተደርጎ የዕለቱ ትምህርተ ወንጌልና ዝማሬ ከቀረበ በኋላ ውዳሴ ማርያም፣ መልክዐ ኢየሱስ ተደግሞ ታቦታ ሕጉ ወደ ተዘጋጀላቸው ድንኳን ይገባሉ /ሠርግው፤ 1981፣ 9/፡፡ በሁለተኛ የአገልግሎት ክፍል ካህናቱ ስብሐተ እግዚአብሔር ሲያደርሱ ያድራሉ፡፡ በመንፈቀ ሌሊትም ሥርዐተ ቅዳሴው ተጀምሮ ከሌሊቱ በ9፡00 ሠርሆተ ሕዝብ ይሆናል፡፡ በነጋታው የሥርዐተ ጥምቀቱ መርሐ ግብር ይቀጥላል፡፡

የከተራ በዓል ምሳሌያት በበዓለ ጥምቀት ዋዜማ የታቦታቱ ወደ ወንዝ መውረድና የባሕረ ጥምቀቱ መዘጋጀት ሃይማኖታዊ ታሪክና ምሳሌ አለው፡፡የቃል ኪዳኑን ታቦት አክብሮ መጓዝና ወደ ወንዝ መወረድ የተጀመረው በአሮን ልጅ በአልዓዛር ጊዜ ነው፡፡ ኢያሱ በሙሴ እግር ተተክቶ ሕዝበ እስራኤልን እየመራ ከዮርዳኖስ ወንዝ ሲደርስ ባሕሩ ከሁለት ይከፈልና ወራጁም ይቆም/ ይከተር/ ነበር፡፡ እስራኤል ዘሥጋ ወደ ምድረ ርስት ለመግባት የዮርዳኖስን ወንዝ ሲሻገሩ፡- ድንኳን ጥለው የቃል ኪዳኑን ታቦት በድንኳን ውስጥ አድርገው ሌዋውያኑ በዙሪያው፣ ካህናቱ ደግሞ በውስጥ ኾነው እግዚአብሔርን እያመሰገኑ አድረው በማለዳ ተሻግረዋል /ኢያሱ 3÷8-9/፡፡ ካህናቱ የቃል ኪዳኑን ታቦት አክብረው የወንዙን ዳርቻ በረገጡት ጊዜ እንደ ክረምት ማዕበል ይወርድ የነበረው ውኃ ግራና ቀኝ ተከፍሎ እንደ ግድግዳ ወደ ላይ ቆሟል፡፡ ሕዝቡ ተሻግሮ እስከሚያበቃ ታቦተ ጽዮንን ያከበሩት ካህናት ከወንዙ መሀል ይቆሙ ነበር፡፡ በዚህ መሠረት ‹‹ወተጠምቃ እገሪሆሙ ለካህናት›› ይህም‹‹የካህናት እግሮቻቸው የዮርዳኖስን ውኃ በመርገጣቸው እንደ ጥምቀት ሆናቸው›› በሐዲስ ኪዳነ ጌታችን ለመሠረተው ሥርዐተ ጥምቀት ምሳሌ ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የጥምቀትን ዋዜማ ከተራ ብላ የጠራችው ከዚህ በመነሣት ነው፡፡ ጌታችን በተጠመቀ ጊዜ የዮርዳኖስ ወንዝ የላይኛው ሸሽቶ ወደ ላይ ተመልሶ ሽቅብ ፈሷል፡፡ የታቹም ወደ ታች ሸሽቷል፡፡ የላይኛው ፈሳሽ ተቋርጦ እንደ ክምር ተቆልሎ ቀርቷል።ቅዱስ ዳዊት የተመለከተውም ይህንኑ ነው። ከአዳም ጀምሮ እስከ ክርስቶስ ድረስ በዘር ይወርድ የነበረው ፍዳ መርገም በክርስቶስ ቤዛነት ተቋርጦ ፤ የታቹም ፈጽሞ መድረቁ ኃጢአተ አዳም የመጥፋቱ ምሳሌ ነው፡፡ እስራኤል ፈለገ ዮርዳኖስን ተሻግረው ወደ ኢያሪኮ መሔዳቸው ምእመናን በጥምቀት ከኃጢአት ቍራኝነት ተላቀው እግራቸውን ወደ ልምላሜ ገነት ወደ ዕረፍት መንግሥተ ሰማያት አቅንተው ለመሔዳቸው ምሳሌ ነው፡፡

ኢያሱ የጌታ፣ እስራኤል የምእመናን፣ ዮርዳኖስ የጥምቀት፣ ምድረ ርስት የገነት መንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፡፡ ታቦቱን አክብሮ የሚሔደው ካህን የቅዱስ ዮሐንስ፣ታቦቱ የጌታችን፣ ባሕረ ጥምቀቱ የዮርዳኖስ ወንዝ፣ ታቦታቱን አጅበው የሚሔዱትና በዓሉን የሚያከብሩት ምእመናን ወደ ቅዱስ ዮሐንስ እየመጡ የንስሐ ጥምቀት ሲጠመቁ የነበሩት ሰዎች ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ታቦታቱ በጥምቀት ዋዜማ ከመንበራቸው ወደ ጥምቀተ ባሕር መውረዳቸውና በዚያ ማደራቸው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእደ ዮሐንስ በፈለገ ዮርዳኖስ ከማታው ጀምሮ መውረዱንና ተሰልፎ ተራውን ሲጠብቅ ማደሩን ያጠይቃል፡፡ ‹‹ጥምቀት የሞቱና የትንሣኤው ምሳሌ ነው፡፡ ከኃጥአን ጋር ተቆጥሮ እንዲጠመቅና እንዲሰቀል የተጻፈውን ቃል ንስሐና ጥምቀት የማያስፈልገው ሲሆን ነገር ግን ፍጹም ኃጥእ መስሎ በዮሐንስ እጅ ጥምቀትን ለመፈጸም በማየ ዮርዳኖስ እግር ተጠመቀ፡፡›› /ኪ.ወ.ክ ፤517/፡፡ ጌታችን የተጠመቀበት ወርኀ ጥር በእስራኤላውያን ዘንድ የዝናብ፣ የበረዶ ወራት ነው፡፡ ከወንዝ ዳር ያለ መጠለያ መዋልና ማደር አይቻልም፡፡ በመኾኑም ከዮሐንስ ለመጠመቅ የሚሄዱ ሰዎች ሁሉ በዮርዳኖስ ዙሪያ ድንኳናቸውን ተክለው ያርፉ ነበር፡፡ በዚህ አንጻር ዛሬም በባሕረ ጥምቀት ዙሪያ ድንኳኖች ዳሶች ይጣላሉ፡፡እኛ በዚህ ወቅት ታቦት ይዘን፣ ከወንዝ ወርደን፣ ድንኳን ተክለን በማክበራችን ይፈጸማል፡፡

መልካም የጥምቀት በዓል

በዓለ ጥምቀት

በዓለ ጥምቀት

 

ጥምቀት አጥመቀ አጠመቀ (ነከረ) ከሚለው የግዕዝ ቃል የወጣ ሲሆን ትርጉሙም መጠመቅ መነከር ማለት ነው:: በዚህም ምስጢር ከእግዚአብሔር በመንፈስ እንወለዳለን ::

የጥምቀት ምሳሌ በብሉይ ኪዳን ተጠቅሶ ይገኛል::

  1. የሕዝበ እስራኤል ቀይ ባሕርን መሻገር:: <<ሁሉም በባህር መካከል ተሻገሩ ሁሉም ሙሴን ይተባበሩ ዘንድ በደመናና በባህር ተጠመቁ>> 1 ቆሮ 10:2 ዘጸ 14:22
  2. ኖህና ቤተሰቡ በእምነት መርከብ ሰርተው ከጥፋት ውኃ መዳናቸው 1 ጴጥ 3: 20-21
  3. በኢያሱ የምስፍንና ዘመን የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳን ታቦት የተሸከሙት የካህናት እግሮች በውሃ ዳር ሲጠልቁ ከላይ የሚወርደው ውሃ ቆሞ እስራኤል ዮርዳኖስን በደረቅ መሻገራቸው 2 ኢያ 3፡15

ከዚህ ቀጥለን የወልድን ጥምቀት (ጥምቀተ ወልድ) እናያለን

ጌታችን ከእመቤታችን በኅቱም ድንግልና ተጸንሶ በኅቱም ድንግልና ተወለደ:: በተወለደ በ 40 ቀኑ ዕጉለ ርግብ ዘውገ መዕነቅ ይዞ ቤተ እግዚአብሔር በመግባት በመውጣት ሕገ መጽሐፋዊን ሕገ ጠባዕያዊን ሲፈጽም ‘በበህቅ ልህቀ እንዘ ይትኤዘዝ ለአዝማዲሁ እንተ ይእቲ እሙ’ እንዲል (ሉቃ 2:51):: ለእናቱ እየታዘዘ አድጎ 30 ዓመት ሲሞላው ወደ ዮርዳኖስ ሄደ:: ዕለቱ ማክሰኞ ሰዓቱ 10 ሰዓት ሌሊት ነው:: ዮሐንስን አጥምቀኝ አለው:: ዮሐንስም ጌታዬ እኔ ባንተ ልጠመቅ ይገባኛል እንጅ አንተ በእኔ አንዴት ትጠመቃለህ አለው::ጌታም መልሶ ሕግን ሁሉ ልንፈጽም ይገባናልና አለው:: አንድም ጥምቀት አንዲት መሆኗን ያመለክታል::

ዮሐንስም መልሶ ሌላውን በአንተ ስም አጠምቃለሁ አንተን በማን ስም ላጥምቅህ አለው:: ጌታችንም እንዲህ አለው ‘ወልዱ ለቡሩክ ከሣቴ ብርሃን ተሣሃለነ’ እያልክ አጥምቀኝ አለው:: ዮሐንስም እሺ አለ:: ጌታችንም ሊጠመቅ ከዮርዳኖስ ባህር ውስጥ ሲገባ የነቢዩ ቃል ይፈጸም ዘንድ ዮርዳኖስ ወደ ኋላ ሸሸች በመዝሙር 113:5 ‘ባህርኒ ርእየት ወጎየት ወዮርዳኖስኒ ገብአ ድኅሬሁ አድባር አንፈርአጹ ከመሐራጊት። ትርጉም ‘አንቺ ባሕር የሸሸሽ አንቺም ዮርዳኖስ ወደ ኋላሽ የተመለሽ ምን ሆነሻል:: እናንተም ተራሮች እንደኮርማዎች ኮረብቶችሽ እንደጊደር ለምን ዘለላችሁ’ የተባለው የነቢዩ ቃል ይፈጸም ዘንድ::

ጌታ ሲጠመቅ ተራሮች ሽቅብ ዘለሉ ውሆች ተናወጹ የመጣው ፈጣሪያቸው አምላካቸው ነውና:: በኋላ ግን በሰውነቱ ተናግሮ በአምላክነቱ አጽንቷቸው በእደ ዮሐንስ ተጠመቀ:: ተጠምቆ ከውሃ ሲወጣ በማቴ 3:13 -17 እንደተጻፈው አብ በደመና ሆኖ ‘ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ሎቱ ስምዕዎ’ የምወደው ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት ብሎ የባህርይ ልጅነቱን መስክሮለታል:: መንፈስ ቅዱስም በአምሳለ ርግብ ፀዓዳ ሆኖ ወርዶ በራሱ ላይ አርፎበታል::

፩. ከፍ ብሎ በ 31 ዝቅ ብሎ በ 29 ዓመት አለመጠመቁ በ 30 ዓመቱ መጠመቁ አዳም የ 30 ዓመት ጎልማሳ ሆኖ በ 40 ቀን አግኝቶ ያጣትን ልጅነት ለማስመለስ ነው::

፪. አምላክ ሰው ሲሆን በሰው እጅ መጠመቁ ትህትናውን ለመግለጽ ነው::

፫. ዮሐንስን አስጠርቶ ካለበት ቦታ መጠመቅ ሲችል ዮሐንስ ወዳለበት ወደ ገሊላ ሄዶ መጠመቁ ሥርዓትን ለማስተማር ነው:: ምክንያቱም ዮሐንስን አስጠርቶ ተጠምቆ ቢሆን ኖሮ ዛሬ መኳንንቱ መሳፍንቱ ባለስልጣናቱ እቤታችን ድረስ መጣችሁ አጥምቁን ባሉ ነበር::

፬. በማር በወተት መጠመቅ ሲችል በውሃ የተጠመቀበት ምክንያት ማር ሲልሱት ወተትም ሲጠጡት እንጅ ሊታጠቡባቸው አልተፈጠሩምና:: አንድም በማር በወተት ተጠምቆ ቢሆን ኖሮ ማርና ወተትን ድሆች ስለማያገኟቸው ሳይጠመቁ ይቀሩ ነበርና:: ጥምቀት የተሰራ ለሁሉም ሰው ነውና ደሃውም ሀብታሙም በሚያገኘው በውሃ ተጠመቀ:: አንድም በውሃ የተጠመቀበት ምክንያት ውሃ ቢጠጡት ያረካል በታጠቡበት ያነጻል ጥምቀትም ከኃጢአታችን ያነጻናልና:: ጥምቀትም ከሥላሴ መወለዳችንን ቁልጭ አድርጎ ያሳያልና::

፭. ብዙ ባሕር እያለ የዮርዳኖስን ባሕር የመረጠው የዕዳ ደብዳቤያችንን ሊያጠፋልን ነው:: ምክንያቱም ዲያብሎስ አዳምና ሔዋንን የጨለማ መጋረጃ ጋርዶ ‘አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ ሔዋን ዓመቱ ለዲያብሎስ’ ብላችሁ ጽፋችሁ ብትሰጡኝ አገዛዜን አቀልላችሁ ነበር ሲላቸው ይህንን ጽፈው ሰጡት:: ዲያብሎስ ያንን በሁለት ቀርጾ ጽፎ አንዱን በዮርዳኖስ አንዱን በሲኦል ጥሎት ነበርና በዮርዳኖስ የጣለውን እንደሰውነቱ ረግጦ እንደምላክነቱ አቅልጦ አጥፍቶልናል:: በሲኦል የጣለውን ጌታ በዕለተ ዐርብ በተሰቀለ ጊዜ በአካለ ነፍስ አጥፍቶልናል:: ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ <<በጥምቀትም ከእርሱ ጋር ተቀብራችሁ በጥምቀት ደግሞ ከሙታን ባስነሣው በእግዚአብሔር አሠራር በማመናችሁ ከእርሱ ጋር ተነሣችሁ። እናንተም በበደላችሁና ሥጋችሁን ባለመገረዝ ሙታን በሆናችሁ ጊዜ ከእርሱ ጋር ሕይወትን ሰጣችሁ። በደላችሁን ሁሉ ይቅር አላችሁ። በእኛ ላይ የነበረውን የሚቃወመንንም በትእዛዛት የተጻፈውን የዕዳ ጽሕፈት ደመሰሰው። እርሱንም በመስቀል ጠርቆ ከመንገድ አስወግዶታል።>> እንዳለን ቆላ ፪:፲፪-፲፬

ሌሊት በ 10 ሰዓት መጠመቁ ምስጢረ መንግስቱን ለመግለጽ ነው:: በቀን ተጠምቆ ቢሆን ኖሮ መንፈስ ቅዱስ በአምሳለ ርግብ ሲወርድ ሰዎች ይህ መናኛ ርግብ እንጅ መንፈስ ቅዱስ አይደለም ይሉ ነበር::

የተወደዳችሁ ሕዝበ ክርስቲያን:- በየዓመቱ የምናከብረው የጥምቀት በዓል ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ጥምቀት አንዲት ናት አንዳለው (ኤፌ ፬:፭) አባቶችም በሃይማኖት ጸሎት ላይ ወነአምን በአሀቲ ጥምቀት ለሥርየተ ኃጢአት ብለው እንዳስተማሩን ጥምቀት አንዲት የማትደገም የማትከለስ መሆኗን አምነን ከጥምቀት በዓሉም በረከት ለማግኘት ነው:: የአባቶቻችን አምላክ ልዑል እግዚአብሔር በዓሉን የሰላም የፍቅር ያድርግልን:: ከበዓለ ጥምቀቱም በረከት ረድኤት እንዲከፍለን የእናታችን የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን።

የደብሩ አገልጋይ መምህር በቃሉ ዳዊት

ይእዜኒ ለሰላም ንትልዋ እስመ ተወልደ ክርስቶስ

ይእዜኒ ለሰላም ንትልዋ እስመ ተወልደ ክርስቶስ

በመልአከ ምህረት ቆሞስ አባ ወልደጊዮርጊስ አየለ

ቅዱስ ያሬድ “ይእዜኒ ንትልዋ ለሰላም፤ እንግዲህስ ሰላምን እንከተላት” በማለት ለሰው ልጆች ሁሉ ታላቅ ጥሪ አቅርቧል። ቅዱሱ ይኽን ታላቅ መንፈሳዊ ጥሪ ያቀረበው ለልደት በሚዘመረው ሰላም በተባለው የዚቁ ክፍል ነው። ለሰላም ጥሪ ያቀረበበትንም ምክንያት “እስመ ተወልደ ክርስቶስ ዮም በዛቲ ዕለት ፍሥሐ ንዜኑ ለዘየአምን ዜና ሠናየ ዘውእቱ ሕፃን ኃይሎሙ ወፅንዖሙ ለእስራኤል፤ በዚች ዕለት ክርስቶስ ተወልዷልና ለሚያምኑት ሁሉ ደስታን መልካም የምሥራችንም እናወራለን። ይኽም የተወለደው ሕፃን ለእስራኤል ብርታታቸውና ኀይላቸው ነው” በማለት አብራርቶታል።ቅዱስ ያሬድ ምልጣን በተባለው የዚቁ ክፍልም “ይእዜኒ ለሰላም ንትልዋ፤ መድኃኒነ ተወልደ ነዋ፤ መድኃኒታችን ተወልዷልና አንድም ስለተወለደ እንግዲህስ ሰላምን እንከተላት” ብሏል።

ቅዱስ ያሬድ በሰላሙም ሆነ በምልጣኑ ሰላምን እንከተል ላለው ጥሪው ዐቢይ ምክንያቱ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መወለድ ነው። የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም መወለድ በዓለሙ ውስጥ ያመጣቸው በርካታና መሠረታዊ ለውጦች አሉ። ከእነዚህም መካከል አንዱ ሰላም ነው።

አዳምና ሔዋን በበደሉበት ወቅት ካጧቸው ጸጋዎች መካከል አንዱ ሰላም ነው። ሰላማቸውን አጥተዋልና አጽናኝና አረጋጊ የሆነውን የተሰበረውን የሚጠግነውን የእግዚአብሔን ድምፅ በገነት መካከል ሲመላለስ በሰሙበት ወቅት ፈሩ። ከእግዚአብሔር ዐይን የማይሸሽጋቸውን ቁጥቋጦ ይሸሸጉበት ዘንድ ተመኙ። ልጃቸው ቃኤንም ወንድሙን ገድሎ ሰላም በራቀው ወቅት ማንም በሌለበት ሀገር ‘’የሚያገኘኝ ሁሉ ይገድለኛል” አለ።

ሰው ሰላሙ የሚሰጠው ከእግዚአብሔር ብቻ ነው። ከእግዚአብሔር በክህደት፣ በኑፋቄና በበደል የተለየ ሰው ሰላም የለውም። በብዙ አዝማድ ቢከበብ፣ ዘመናዊ የጦር መሣርያ የታጠቁ ሠራዊት ቢኖረው፣ ኃያላን በማይበረታቱበት ቅፅር ቢኖር ከእግዚአብሔር ጋር አንድነት የሌለው ሰው ሰላም የለውም። እንዲህ ዓይነቱ ሰው ከውጪ ሲታይ ሰላማዊ መስሎ ቢታይ እንኳ የልብ ሰላም ግን የለውም።

ቅዱሳኑ ግን በነፍስም በሥጋም ኅብረታቸው ከእግዚአብሔር ጋር ስለሆነ ሰዎችን ሁሉ የሚያሸብር መከራ በዓለም በሚከሰትበት ወቅት አይሸበሩም። ታዳጊያቸውና ሰላማቸው እግዚአብሔር የማያንቀላፋ ትጉህ እረኛቸው ከእነርሱ ጋር መሆኑን ስለሚያውቁ ተረጋግተው ይኖራሉ። የእግዚአብሔር ወዳጅ የሆነው ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “በሞት ጥላ መካከል እንኳ ብሄድ፣ አንተ ከእኔ ጋር ነህና ክፉን አልፈራም፣ በትርህና ምርኩዝህ እነርሱ ያጽናኑኛል” ብሏል። መዝ. ፳፪፣፬። ልጁ ጠቢቡ ሰሎሞንም በተግሣፅ መጽሐፉ “ኃጥእ ማንም ሳያሳድደው ይሸሻል፣ ጻድቅ ግን እንደአንበሳ ተማምኖ ይኖራል” ብሏል። ተግሣጽ ፬፣፩።

ከዚህ እውነታ በመነሣት የአምስት ሺህ አምስት መቶ ዓመታት የሰው ልጆች ኑሮ ምን ይመስል እንደነበር ለመገመት አያስቸግርም። ሰው ከፈጣሪው ርቆ ልጅነቱን አጥቶ ሞት ተፈርዶበት ሰላሙን ተቀምቶ ይኖር ነበር። ጽድቁ እንደ መርገም ጨርቅ ሆኖበት ጉልበቱ ደካማ ጸሎቱ የማይሰማ ነበር። ይኽንን ያጣውን ጸጋና በረከት ደግሞ በራሱ ጥረት ፈጽሞ ሊያመጣው ወይም መልሶ ሊያገኘው አልቻለም ነበር።

ይህን የሰው ልጆችን መከራ በእውነት የተመለከተ እግዚአብሔር የሰላም ባለቤት የሆነውን ልጁን ጌታችን ኢየሱስ ከርስቶስን ወደ ዓለም ሊልከው ወደደ። ለዚህም አስቀድመው ነቢያቱ ትንቢት ተናገሩ። ነቢየ ልዑል ኢሳይያስ “ሕፃን ተውልዶልናልና፣ ወንድ ልጅም ተሰጥቶልናልና፤ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል።ስሙም ድንቅ መካር ኀያል አምላክ፣ የዘላለም አባት፣ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል” በማለት ተናግሯል። ኢሳ. ፱፣፮።

እግዚአብሔር አስቀድሞ ለሥጋዌው የወሰነው ዘመን ደርሶ ያስቆጠረውን ሱባኤና ያናገረውን ትንቢት ሊፈጽም፣ ያስመሰለውንም ምሳሌ እውን ሊያደርግ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷም ነፍስ ነስቶ ያለ ዘርኣ ብእሲ በሕቱም ድንግልና ተጸንሶ በሕቱም ድንግልና በተወለደባት ሌሊት በቤተልሄም ሰማይ ልዩ ምስጋና ያቀረቡት የሰማይ መላእክት “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ለዕጓለ እመሕያው ሥምረቱ፤ ክብር ለእግዚአብሔር በሰማያት፣ ሰላምም በምድር፣ ለሰው ልጅም በጎ ፈቃድ ሆነ” በማለት አመስግነዋል። ሉቃ. ፪፣፲፬። መላእክቱ በዚህ ምስጋናቸው ኢሳይያስ የሰላም አለቃ ብሎ የተናገረለት አምላካችን አማኑኤል በእኛ ባሕርይ በመካከላችን በመገኘቱ አጥተነው የነበርነው ሰላማችን ወደ እኛ መምጣቱን አብሥረዋል። እንዲያውም ቅዱስ ሉቃስ እንደጻፈው ከምስጋናቸው አስቀድሞ አንዱ መልአክ በታላቅ ክብርና ግርማ ተገልጦ “ወይቤሎሙ መልአክ ኢትፍርሁ እስመ ናሁ እዜንወክሙ ዐቢየ ዜና ዘይከውን ፍሥሓ ለክሙ ወለኵሉ ዓለም፤እስመ ናሁ ተወልደ ለክሙ ዮም መድኅን ዘውእቱ ክርስቶስ እግዚ ቡሩክ በሀገረ ዳዊት፤ እነሆ ለእናንተና ለሕዝቡ ሁሉ ደስታ የሚሆን ታላቅ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ፤ እነሆ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኅን ተወልዶላችኋል፣ ይኸውም ቡሩክ ጌታ ክርስቶስ ነው።

እንግዲህ መልአኩ የተወለደው ጌታ ክርስቶስ መሆኑን የእርሱም የልደቱ ዜና ታላቅ የምሥራች መሆኑን አስረድቶ ሲያበቃ ተከትለውት ከመጡት መላእክት ጋር “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት፣ ወሰላም በምድር ሥምረቱ ለሰብእ” እያለ ወደ ማመስገን ሄደ። ይኽም በጌታችን ልደት የሰው ልጅ ለዘመናት ሲናፍቀው የኖረውን ሰላም ማግኘቱን ያስረዳል። አባታችን ቅዱስ ያሬድም ከመልአኩ በተረዳው መሠረት “ይእዜኒ ለሰላም ንትልዋ፤ እንግዲህስ አንድም አሁንስ ሰላምን እንከተላት ለምን ትለኝ እንደሆነ “መድኀኒነ ተወልደ ነዋ፤ መድኃኒታችን ተወልዷልና” ብሎ ዘመረ።

ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ የታነፀች የማዕዘኗ የራስ ድንጋይዋ ደግሞ ክርስቶስ የሆነላት አማናዊት ቤተ ክርስቲያን ናት። በመሆኑም በነቢያት ትንቢት ተነግሮለት የተወለደውን ሐዋርያት በዓለሙ ዙረው ወንጌለ መንግሥቱን የሰበኩለትን ሰማዕታት ስለስሙ ምስክርነት ንጹሕ ደማቸውን ያፈሰሱለትን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ልደት በየዓመቱ በደመቀና በታላቅ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ታከብራለች። በዓሉን ማክበር ብቻ ሳይሆን በልደቱ ለሰው ልጆች የተሰጠው ታላቁ አምላካዊ ጸጋ ማለት ሰላም ከልጆቿ ሕይወት እንዳይታጣም አበክራ ታስተምራለች።

ሰላም ለማንኛውም ሰው መንፈሳዊውም ሆነ ምድራዊ ሕይወት መሠረት ነው። የእያንዳንዱ ሰው ሕሊና የሚኖርበትም ዓለም ሰላም ካልሆነ ሠርቶ ማግኘት፣ ወልዶ ማሳደግ፣ ነግዶ ማትረፍ፣ ተረጋግቶ ሃይማኖታዊ ሥርዓትን ፈጽሞ ጽድቅን ማግኘት አይኖርም። በመሆኑም ሰው ከራሱ፣ ከቤተሰቡ አባላት፣ ከጎረቤቶቹ፣ ከመላው የማኅበረሰቡ አባላት፣ ከሥነ ፍጥረት ጋር ሰላም ሊሆን ይገባዋል። ሰላምን ለመጠበቅም ዋጋ መክፈል ይኖርበታል። ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ሕስሳ ለሰላም ወዴግና፤ ሰላምን ሻት፣ ተከተላትም” ብሏል። መዝ. ፴፫፣ ፲፬። በሌላ በኩል “መቅደመ ኵሉ ኅሡ ሰላማ ለሀገር፤ ከሁሉ በፊት አስቀድማችሁ የሀገርን ሰላም ሹ” ተብሏል። ይኽ ሁሉ የሚያሳየን ለክርስቲያን ሰላም መሠረታዊና ተቀዳሚ ጉዳይ መኾኑን ነው።

ይሁን እንጂ በአሁኑ ወቅት ሰላም በሀገር፣ በቤተ ክርስቲያን፣ በትዳር፣ በማኅባርዊ ኑሮ እየጠፋ ነው። እያንዳንዱ ግለሰብ ውስጣዊ ሰላም አጥቶ ለጭንቀትና ለአእምሮ ሕመም በመዳረግ ላይ ይገኛል። ምንም እንኳን በዚህ በውጪው ዓለም ቁሳዊው ፍላጎታችን በአንጻራዊነት ሊሟላልን በሚችልበት ዓለም ብንኖርም ካጌጠው ፊታችንና ልብሳችን ጀርባ ያለው ሕሊናችን ግን ሰላምን ፍለጋ ላይ ነው። ለዚህ ደግሞ ዋና መፍትሄው ሰላማችን ወደ ሆነው ወደ ጌታችንና ወደ አምላካችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ በጎ ፈቃዱን በመፈጸም መቅረብ ነው።

የጌታችንን ልደት በምናስብበት ወቅት ራሳችን ከራሳችንና ከሌሎች ጋር ሰላማውያን መሆናችንን መመርመር ያስፈልጋል። በነገር፣ በጥልና በክርክር ተይዞ የጌታችንን ልደት ማክበር ከመሠረታዊ አስተምህሮ ውጪ መሆን ነው፤ በረከትም አያስገኝም። ከዚኽም ጋር ሰላማችንን ያገኘንበትን የጌታችንን ልደት ስናከብር ሰላማቸው በዲያብሎስና በዚኽ ዓለም ጉልበተኞች ተናግቶባቸው ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለው በስደት ያሉትን፣ ታምመው ሰላም አጥተው በየጤና ተቋማቱ የሚንከራተቱትን በማሰብና ሰላማዊው ኢየሱስ ክርስቶስ የረድኤት እጁን እንዲዘረጋላቸው አጥብቀን በመጸለይ ጭምር መሆን አለበት።

ካህናት በቤተ መቅደስ በቅዳሴ ወቅት ዘወትር “ሰላም ለኵልክሙ፤ ሰላም ለሁላችሁ ይኹን” ሲሉን “ከመንፈስህ ጋራ” ብሎ በመመለስ ብቻ ሰላም አይገኝም። ራስን ለክርስቶስ ቃል አስገዝቶ በወንጌል ቃል ተመርቶ በምክረ ካህንና በፈቃደ ካህን ሕይወትን መምራትና ንስሐ ገብቶ በቅዱስ ቁርባን መወሰንን ጭምር ገንዘብ ማድረግ ያስፈልጋል። እስካሁን የነበረውን ጊዜያችንን ከእግዚአብሔር ፈቃድ በራቀ መንገድ ስንመራ ቆይተናል። አሁን ግን ወደ ነፍሳችን እረኛና ሰላማችን ወደሆነው ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ በንስሐ መልሰን በፍቅርና በአንድነት በአንዲት ቤተ ክርስቲያናችን ከሽንገላ በራቀ ከንፈራችን ንጹሕ ምስጋናን ልናቀርብለት ይገባናል። ያለበለዚያ በጥላቻ፣ በሐሜትና በተንኮል ሆነን የምናቀርበውን መሥዋዕት፣ የምንቀበለውን ቁርባን፣ የምናመሰግነውን ምስጋና በአጠቃላይ ማንኛውንም መንፈሳዊ አገልግሎታችንን የቃኤልን መሥዋዕት እንደተጸየፈ ይጸየፍብናል።

ቅዱስ ጳውሎስ “የጨለማን ሥራ ከእኛ እናርቅ” እንዳለው እኛም እግዚአብሔር የማይወደውን የጥልና የክርክር ኑሯችንን ትተን የሰላሙን መንገድ እንከተል። ምክንያቱም “መድኃኒነ ተወልደ ነዋ፤ መድኃኒታችን ተወልዷልና”። ይኽ በቤተልሄም በከብቶች ግርግም በጨርቅ ተጠቅልሎ እንስሳት እስትንፋሻቸውን የገበሩለት መድኃኒታችን የሰላም ባለቤት ነው። ከእኛ ሰላምን ይሻል። ከዚኽም በላይ “አሁን ግን ቀድሞ ርቃችሁ የነበራችሁ እናንተ በኢየሱስ ክርስቶስ ሆናችሁ በክርስቶስ ደም ቀረባችሁ። ሁለቱን አንድ ያደረገ ሰላማችን እርሱ ነውና፣ በሥጋውም በመካከል የነበረውን የጥል ግድግዳ አፍርሶ ጥልን ሻረ። ሁለቱንም አድሶ አንድ ያደርጋቸው ዘንድ በሥርዓቱ የትእዛዝን ሕግ አጠፋ፤ ዕርቅንም አደረገ። በመስቀሉም በአንድ ሥጋው ሁለቱን ወደ እግዚአብሔር አቀረባቸው፤ በእርሱም ጥልን አጠፋ። መጥቶም ቀርበን ለነበርነው ሰላምን ርቃችሁ ለነበራችሁት ለእናንተም ሰላምን ሰጠ” ተብሏል።

በመሆኑም ሰላማችን የተወለደበትን ዕለት ስናከብር የእርሱ መሆናችንንም በምናስብበት ወቅት ሁሉ የሰላም ልጆች መሆናችንን ልናስብና የሰላም ጸር ከሆኑ ድርጊቶች ልንርቅ ያስፈልጋል። ዘወትርም ለእርሱ የምትገዛ ሀገራችንን እግዚአብሔር በምሕረቱ አስቦ ሰላሟን ይጠብቅላት ዘንድ አጥብቀን መጸለይ ይጠበቅብናል። እግዚአብሔር ሰላሙን ለእኛና ለሀገራችን እንዲሁም ለመላው የዓለም ሕዝብ ያድልልን። አሜን።

ህንጻ ቤተክርስቲያን መስራት የሚያሰጠው በረከትና ማድረግ ያለብን ጥንቃቄ

ህንጻ ቤተክርስቲያን መስራት የሚያሰጠው በረከትና ማድረግ ያለብን ጥንቃቄ

ዲ/ን ኅሩይ ውቤ

እግዚአብሔር አምላካችን ሰማይ ዙፋኑ፣ ምርድም የእግሩ መረገጫ ነውና በጊዜና በቦታ አይወሰንም፡፡ ይህ መወሰንና መመርመር የሌለበት አምላካችን ምንጊዜም ፈቃዱን ለሚያደርጉ ሰዎች ቅርብ ነው፡፡ እግዚአብሔር ለሚያምኑበት ቅርብ መሆኑን ከገለጠባቸው መንገዶች አንዱ ደግሞ ምዕመናን በስሙ ተሰብስበው በቤተ መቅደስ ሲጸልዩ ጸሎታቸውን እንደሚሰማ፣ ልመናቸውን እንደሚፈጽም የገባው ዘላለማዊ ቃልኪዳን ነው፡፡ በ2ኛ ዜና መዋዕል 7፡15-16 “አሁንም በዚህ ስፍራ ለሚጸለይ ጸሎት ዐይኖቼ ይገለጣሉ፤ ጆሮቼም ያዳምጣሉ፡፡ አሁንም ስሜ ለዘላለም በዚያ ይኖር ዘንድ ይህን ቤት መርጫለሁ፤ ቀድሻለሁም፤ ዐይኖቼና ልቤም ዘወትር በዚያ ይሆናሉ” ብሏልና፡፡

በብዙ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት አዲስ ሕንፃ ቤተክርስቲያን መስራትና ያረጀውን ማደስ በተደጋጋሚ የሚደረግ መንፈሳዊ ዋጋው ከፍ ያለ የጽድቅ አገልግሎት ነው፡፡ ለዚህም ሰበካ ጉባኤ ሕንጻ አሰሪ ኮሚቴዎች በየቦታው ምዕመናንን በማስተባበር ለመንፈሳዊ ሥራ እንደሚያተጉ ይታወቃል፡፡ ይህን ለማድረግም በቃለ እግዚአብሔር መሰረትነት የታነጸ መንፈሳዊ ግንዛቤ እጅግ በጣም ወሳኝ ነው፡፡ ለዚህም እንዲረዳን ሕንፃ ቤተክርስቲያን ለምን፣ እንዴትና በምን ሁኔታ መሰራት እንዳለበት ከቅዱሳት መፃሕፍት በማጣቀስ ምዕመናንና ምዕመናትን መልካም ለሆነ መንፈሳዊ ፍሬ ለማነቃቃት ይህችን አጭር እናንብባት፡፡

  • ቤተ መቅደስን ለመስራት መመረጥ መታደል ነው

ቤተ መቅደስ የእግዚአብሔር ማደሪያ ነው፡፡ እግዚአብሔር የሚያድርበትን ቤት ለመስራት መታደል ደግሞ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ነው፡፡ በቅዱስ መጽሐፍ ታሪኩ እንደተቀመጠው ነቢየ እግዚአብሔር ንጉስ ዳዊት የእግዚአብሔር ማደሪያ ቤተመቅደስን ሳይሰራ እረፍት እንደማያገኝ በተናገረበት መዝሙሩ እንዲህ ብሎ ነበር፡- “ወደ ቤቴ ድንኳን አልገባም፣ ወደ መኝታዬም አልጋ አልወጣም፣ ለዐይኖቼም መኝታን፣ ለቅንድቦቼም እንቅልፍን፣ ለጉንጮቼም ዕረፍትን አልሰጥም፣ የእግዚአብሔርን ቦታ፣ የያዕቆብ አምላክን ማደሪያ እስካገኝ ድረስ” መዝ. 131፡3-5 ይህንን መልካም ምኞቱን የተረዳ ነቢዩ ናታንም የንጉስ ዳዊትን የእግዚአብሔርን ማደሪያ ለመስራት መነሳሳት አስተውሎ ፈቃደ እግዚአብሔርን ለማወቅ ሱባኤ ገብተዋል፡፡ በ1ኛ ዜና መዋዕል 17፡1-27 ካለው የቅዱስ መጽሐፍ ንባብና በመንፈስ ቅዱስ የተመሩ አባቶቻችን ካስተማሩን ታሪክ እንደምንረዳው ምንም እንኳ ንጉስ ዳዊት እጅግ በርካታ መንፈሳዊ ስራ በመስራት እግዚአብሔርን ያስደሰተ ቢሆንም ጌታ ግን ንጉስ ዳዊት በድካሙ ወራት የሰራውን ኃጢአት አስቦ እንዲጸጸት ቤተ መቅደስ ለመስራት እርሱ እንዳልተመረጠ ነገረው፡፡ ይሁንና የዳዊትን ቅንነት ተመልክቶ ልጁ ሰሎሞን ቤተመቅደስን እንዲሰራ የእግዚአብሔር ፈቃዱ ሆነ፡፡ ከዚህ የምንረዳው ነገር ቢኖር ቤተ መቅደስን ለመስራት መመረጥ እንደ ሰው ሀሳብ ብቻ ሳይሆን እንደ እግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃድ የሚደረግ መሆኑን ነው፡፡ የንጉስ ዳዊትን ኃጢአት አስቦ ቤተ መቅደስን ከመስራት የሚገድብ ቀኖና የሰጠው አምላካችን እግዚአብሔር እኛን ምዕመናንን ቤቱን እንድንሰራ ሲፈቅድልን እንደ ንጉስ ዳዊት “አቤቱ አምላክ ሆይ ለዘላለም የወደድከን፣ እንደ ባለ ማዕረግ ሰው የተመለከትኽን እኛ ማን ነን?” ብለን ልናመሰግነው ይገባል፡፡ ጌታ በደለኞች ስንሆን ይህን በረከት ለእኛ ሲሰጠን “ኀጢአታቸው የተተወላቸው፣ በደላቸውንም ሁሉ ያልቆጠረባቸው ብፁዓን ናቸው” ተብሎ በመዝሙረ ዳዊት 31፡1 የተጠቀሰው የእግዚአብሔር ቃል እውነትነት ስለተገለጠ በደላችንን አይቶ ከዚህ የበረከት አገልግሎት ያልከለከለንን አምላካችንን ልናመሰግነው ይገባል፡፡ ቤተመቅደስን ለመስራት በመመረጣችን ልንደሰትና ቅን አገልግሎትን ልንፈጽም ያስፈልጋል፡፡

  • ምዕመናን ሁላችንም እንደአቅማችን የመሳተፍ ግዴታ አለብን

በቅዱሳት መፃሕፍት ከተቀመጡ መለኮታዊ ትዕዛዛት አንዱ አምላካችንን በፍጹም ልባችን በፍፁም ኃይላችን መውደድ ነው፡፡ እግዚአብሔርን መውደድ ማለት ሀሳባዊ ብቻ ሳይሆን በተግባር የሚገለጥ መሆን አለበት፡፡ በርካታ ቅዱሳን ለእግዚአብሔር ያላቸውን ፍቅር ስሙ የሚመሰገንበት ቤተ መቅደስ በመስራት ገልጸዋል፡፡ እኛም ይህን የማድረግ መንፈሳዊ ግዴታ አለብን፡፡ እስራኤላውያን በምርኮ በነበሩበት ዘመን ቤተ መቅደስን ከመስራት ቸል ባሉ ጊዜ የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ብሎ ወቅሷቸው ነበር፡- “በውኑ ይህ ቤት ፈርሶ ሳለ እናንተ ራሳችሁ በተሸለሙ ቤቶቻችሁ ለመኖር ጊዜው ነውን?” ትንቢተ ሐጌ 1፡4፡፡ ይህ የእግዚአብሔር ቃል እኛንም ይገስጸናል፡፡ ስለሆነም እኛ ባማሩ ቤቶች እየኖርን የእግዚአብሔርን ማደሪያ ከመስራት ቸል ልንል አይገባንም፡፡ ብዙዎቻችን የሰበሰብነውን ገንዘብ የሰጠን አምላካችን መሆኑን ዘንግተን ለመንፈሳዊ አገልግሎት ገንዘብ መስጠትን አክብደን እናየዋለን፡፡ እንደእኛ ለመንፈሳዊ አገልግሎት ንፉግ የነበሩትን እስራኤላውያን የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ብሎ ወቅሷቸው ነበር፡- “እስኪ መንገዳችሁን አስቡ፡፡ ብዙ ዘራችሁ፤ ጥቂትም አገባችሁ፤ በላችሁ፤ ነገር ግን አልጠገባችሁም፤ ጠጣችሁ፤ ነገር ግን አልረካችሁም፤ ለበሳችሁ፤ ነገር ግን አልሞቃችሁም፤ ደመወዙን የተቀበለም በቀዳዳ ከረጢት ሰበሰበ፡፡” ትንቢተ ሐጌ 1፡6፡፡ ያጡትን በረከት እንዲያገኙም እግዚአብሔር እንዲህ አላቸው “በልባችሁ መንገዳችሁን አስቡ፡፡ ወደ ተራራው ውጡ፤ እንጨትንም ቁረጡ፤ ቤቱንም ስሩ፤ እኔም በእርሱ ደስ ይለኛል፤ እመሰገናለሁም፡፡” ትንቢተ ሐጌ 1፡7-8፡፡ ለእግዚአብሔር ቃል የታዘዙ እስራኤል ዘስጋ በዘሩባቤል ተመርተው የአምላካቸውን የእግዚአብሔርን ቤት መስራት ጀመሩ፡፡ እኛም የቅዱሳን በረከት እንዲደርሰን በሕንፃ ቤተክርስቲያን ግንባታው በአቅማችን የመሳተፍ ግዴታችንን መወጣት እንዳለብን የእግዚአብሔር ቃል ይመክረናል፣ ያስተምረናል፡፡

  • የሰይጣንን ፈተና በድል ለመወጣት መዘጋጀት አለብን

ማንኛውም መንፈሳዊ አገልግሎት የበጎ ነገር ጠላት ከሆነ ከዲያብሎስ የሚነሳ ፈተና አያጣውም፡፡ ለዚያ ነው አባቶቻችን “ያለ መከራ ጸጋ አይገኝም” በማለት የሚያስተምሩን፡፡ ሕንፃ ቤተክርስቲያን ለመስራት ስንነሳ በብዙ መልኩ የሚመጣ የሰይጣን ፈተና እንደሚኖር ተገንዝበን ራሳችንን በመንፈሳዊ ኃይልና ጥበብ ማዘጋጀት፣ እግዚአብሔርንም መማጸን አለብን፡፡ ከፈተናዎች የመጀመሪያ ሊሆን የሚችለው የተስፋ መቁረጥ ፈተና ነው፡፡ ስራው ረጅምና ከባድ በሆነ ቁጥር ተስፋ የሚቆርጥ ሰው ሊበዛ ይችላል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ነህምያ የኢየሩሳሌምን የፈረሱ ቅጥሮች፣ የተቃጠሉ በሮች ጉዳይ ሰምቶ በፆምና በጸሎት እግዚአብሔርን እየለመነ ወገኖቹን እስራኤላውያንን “አሁንም ከእንግዲህ ወዲህ መሳለቂያ እንዳንሆን የኢየሩሳሌምን ቅጥር እንሥራ” ባላቸው ጊዜ ለበጎ ሥራ እጆቻቸውን ያበረቱ እንደነበሩ ሁሉ በሚሰሩት ላይ በንቀት የሚስቁባቸውም እንደነበሩ መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምረናል፡፡ በንቀት በሚስቁት ሰዎች ያልተሸነፈው ነቢየ እግዚአብሔር ነህምያም “የሰማይ አምላክ ያከናውንልናል፤ እኛም ንጹሓን ባሪያዎቹ ተነስተን እንሰራለን” መጽ. ነህ. 2፡20 በማለት እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ የሰይጣንን ፈተና በድል ለመወጣት እንደምንችል አብነት የሚሆን ታሪክ ሰርቶ አልፏል፡፡ እኛም አዲሱን ሕንፃ ቤተክርስቲያናችንን ስንሰራ እግዚአብሔርን ተስፋ በማድረግ በመንፈሳዊ ኃይልና ብርታት ልንነሳ ይገባል፡፡

 

  • የጽድቅ አገልግሎታችን በአሰራር ችግር መንፈሳዊነቱን እንዳያጣ መጠንቀቅ አለብን

ሕንፃ ቤተክርስቲያንን መስራት የተቀደሰ ስራ ስለሆነ የተቀደሰ አሰራር ይፈልጋል፡፡ የጽድቅ አገልግሎት መንፈሳዊ በሆነ አመራር መደገፍ አለበት፡፡ በአንዳንድ ቦታዎች ሕንፃ ቤተክርስቲያን ለመስራት የሚሆን ገንዘብ ለመሰብሰብ መንፈሳዊ አሰራርን የሚቃረን አካሄድ እንደሚደረግ ይታወቃል፡፡ ሕንፃ ቤተክርስቲያን ለመስራት የሚውል ገንዘብ ለመሰብሰብ ከመንፈሳዊ አሰራር መራቅ የለብንም፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉ” ዮሐ. 2፡16 በማለት አይሁድን የወቀሳቸው ተመሳሳይ ስራ እየሰሩ እግዚአብሔርን ስላሳዘኑ ነበር፡፡ ስለሆነም እኛ ሕንፃ ቤተክርስቲያን ለመስራት በምናደርገው ጥረት ከሕንፃ ቤተክርስቲያን በላይ የከበረ የእግዚአብሔርን ቃል የሚቃረን አሰራር እንዳንከተል አካሄዳችንን በጥንቃቄ መመርመር ይጠበቅብናል፡፡ ቃሉን ስንጠብቅ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ይሆናል፡፡ “እግዚአብሔር ቤትን ካልሰራ ቤትን የሚሰሩ በከንቱ ይደክማሉ” መዝ. 126፡1 እንደተባለ ከቃለ እግዚአብሔር ጋር የሚጣላ አሰራር ከተከተልን ግን ድካማችን ዋጋ የሌለው ይሆንብናል፡፡

  • ሕንፃ ቤተክርስቲያን ለሰው ይሰራል እንጂ ሰው ስለ ሕንፃ ቤተክርስቲያን አልተፈጠረም

ብዙ ቦታዎች ላይ በተደጋጋሚ ከሚስተዋሉ ችግሮች ውስጥ አንዱ ሕንፃ ቤተክርስቲያንን ለመስራት በሚል ሰበብ መንፈሳዊ አገልግሎትን ቁሳዊ ማድረግና የቤተክርስቲያንን ዋነኛ ተልዕኮ መዘንጋት ነው፡፡ ሕንፃ ቤተክርስቲያንን መስራት ክብር የሚሆነው ሕንፃ ሥላሴን (ምዕመናንና ምዕመናትን) በእምነትና በምግባር ለማሳደግ ስንጠቀምበት ብቻ ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ዋና ተልዕኮዋን ዘንግታ ፎቅና ሕንፃ በማሳመር ብቻ መጠመድ የለባትም፡፡ ሕንፃ ቤተክርስቲያን ለሰው ይሰራል እንጂ ሰው ስለ ሕንፃ ቤተክርስቲያን አልተፈጠረምና፡፡ ስለሆነም ለሕንጻ ቤተክርስቲያን ገንዘብ ለማሰባሰብ ሲባል የእግዚአብሔርን ቅዱስ ቃል በቃሉ ለሚነግዱ ምንደኞች፣ ለፖለቲከኞች፣ ለዘረኞችና ለእወደድ ባይ “አገልጋዮች” ዓላማ መሸቀጥን ልንከላከል ይገባል፡፡ ቃሉን ጠብቀን ስናገለግል እግዚአብሔር የሰማያዊት ኢየሩሳሌም አምሳል የሆነች ሕንፃ ቤተክርስቲያንን በእኛ አድሮ ይሰራል፡፡ በቁሳዊ እይታ ተጠምደን ቃሉን ችላ ስንል ግን እግዚአብሔር ከእኛ ይለያል፡፡ እግዚአብሔር የሌለበት ሕንፃ ደግሞ ቁሳዊ እንጂ መንፈሳዊ ዋጋ የለውም፡፡ የተወደደ ሐዋርያ ቅዱስ ዮሐንስ እንዳስተማረን “ፍጹም ዋጋ እንድታገኙ እንጂ የሠራችሁትን እንዳታጡ ራሳችሁን እወቁ፡፡” (2ዮሐ. 1፡8) ተብለናልና በምናደርገው መንፈሳዊ አገልግሎት ፍጹም ዋጋ ለማግኘት እንድንችል የሠራነውን ከሚያሳጡ፣ ከመንፈሳዊ አሰራር ከሚያወጡ አካሄዶች ርቀን በፍጹም መንፈሳዊ ፍቅርና መታዘዝ የሰማያዊት ኢየሩሳሌም አምሳል የሆነች ሕንፃ ቤተክርስቲያንን ለመስራት ልንፋጠን ይገባል፡፡ በዚህም የቅዱሳንን በረከት እንካፈላለን፡፡

አምላካችን እግዚአብሔር በመንፈሳዊ ኃይል አነሳስቶ ሕንፃ ቤተክርስቲያናችንን ሰርተን ለመፈጸም ያብቃን፡፡ ለዚህም የእመቤታችን አማላጅነት፣ የሊቀ መላዕክት ቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት አይለየን፡፡