ሆሣዕና
ሆሣዕና
በመጋቤ ሐዲስ ፍቅረ ማርያም ባዘዘው
በቦሌ መንበረ ብርሃን ቅዱስ እግዚአብሔር አብ ቤተክርስቲያን የሐዲስ ኪዳን የትርጓሜ መምህር
ፍትሕዎን ወአምጽእዎን ሊተ
ፈትታችሁ አምጡልኝ ማቴ.21፤2
ዐቢይ ጾም ከገባ ይህ ስምንተኛ ሳምንት ሲሆን ዕለቱም ሆሳዕና ተብሎ ይጠራል፡፡ ይህም ሲባል የዓለም መድኃኒት መሆኑን ወይንም ሰውን ለማዳን ሰው የሆነበት ሰማያዊ ምሥጢር የሚነገርበት ቀን ነው፡፡ ቅዱስ ወንጌል እንዲህ ይላል፡- ወደ ኢየሩሳሌምም ቀርበው ወደ ደብረ ዘይት ወደ ቤተ ፋጌ ሲደርሱ፥ ያንጊዜ ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ሁለት ላከ፥ እንዲህም አላቸው፦ በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሂዱ፥ በዚያን ጊዜም የታሰረችን አህያ ውርንጫም ከእርስዋ ጋር ታገኛላችሁ፤ ፈትታችሁ አምጡልኝ። ማንም አንዳች ቢላችሁ። ለጌታ ያስፈልጉታል በሉ፤ ወዲያውም ይሰዳቸዋል። ለጽዮን ልጅ። እነሆ፥ ንጉሥሽ የዋህ ሆኖ በአህያ ላይና በአህያይቱ ግልገል በውርንጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል በሉአት ተብሎ በነቢይ የተነገረው ይፈጸም ዘንድ ይህ ሆነ። ደቀ መዛሙርቱም ሄደው ኢየሱስ እንዳዘዛቸው አደረጉ፥ አህያይቱንና ውርንጫዋንም አመጡለት፥ ልብሳቸውንም በእነርሱ ላይ ጫኑ፥ ተቀመጠባቸውም።
እንደሚታወቀው አካላዊ ቃል ሰው የሆነበት ምሥጢር በመከራ ውስጥ የነበረውን የሰው ዘር በሙሉ በሞቱ ሞትን ድል ነሥቶ ከባርነት ቀንበር ነጻ ለማውጣት ነበር፡፡ የሰው ልጅ ከእግዚአብሔር ሕግ ይልቅ ለራሱ የፈቃድ ሕግ የተገዛ በሞት ጥላ ውስጥ ሲርመሰመስ የነበረ፤ የብርሃንን ጮራ በተስፋ የሚጠባበቅ ከመከራው የተነሣም ሁለንተናው በኃጢአት የጠቆረ ሆኖ እንዲህ የሚልን ድምጽ ሲያሰማ የነበረበት ወቅት ነበር፡፡ ኢትርአያኒ እስመ አነ ጸላም እስመ ኢርአየኒ ፀሐይ መሐልይ.1፤6 ጥቁር ነኝና አትዩኝ ፀሐይ አላየኝምና፡፡ ይህ የሚገልጸው ሰዎች እንዴት ባለ የመከራ ሕይወት ውስጥ ማለፋቸውንና ከመከራው ጽናት የተነሣ ጥቁር ነን አትዩን መከራው አጥቁሮናል የእኛ መልክ የሚያምረው ውብ የሚሆነው ፀሐይ ሲወጣ ነው አሁን ጊዜው ጨለማ ነው ፀሐይ አልወጣም በማለት ክርስቶስ ፀሐየ ጽድቅ እርሱ ሰው እስኪሆን በተስፋ ደጅ ይጸኑ ነበር፡፡ ፀሐይ ኢየሱስ ክርስቶስ ከምሥራቅ ድንግል ማርያም እስኪወጣ በተስፋ ሲማጸኑ ኑረዋል፡፡ ጊዜው ሲደርስ ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም ተወለደ፡፡ በነፍሱም በሥጋውም በኃጢአት የታሰረውን ሰው ይፈታው ዘንድ ሁለቱን ደቀ መዛሙርት ወደ ታሰሩት ላከ፡፡ የሚገርመው ነገር ደግሞ የታሰሩት ሁለት ናቸው የተላኩትም ሁለት ናቸው፡፡ ሁለቱ በእስራት ውስጥ የነበሩት ነፍስና ሥጋ ናቸውና፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም ክድንግል ማርያም የነሣው ሁለቱን ነፍስና ሥጋን ነው ለምን ሲባል ሁለቱም ድኅነት ይፈልጉ ነበርና፡፡ ነፍስና ሥጋን አልነሣም ከተባለ ግን አዳም በነፍሱም በሥጋውም አልዳነም ማለት ነው፡፡
ሁለቱ አዳምና ሔዋን እንዲሁም ሁለቱ ነፍሥና ሥጋ ከታሰሩበት ዓለም ከተባለ መንደር ሁለቱ knowledge and wisdom ( እውቀትና ጥበብ) የተባሉ ደቀ መዛሙርት የታሠሩትን ፈትተው ያመጡ ዘንድ ተላኩ የሚገርመው ነገር የሚከራከራችሁ ቢኖር ለጌታ ያስፈልጉታል ወይንም ጌታቸው ይፈልጋቸዋል በሉ አላቸው፡፡ በነፍስም በሥጋም አክብሮ የፈጠረን እርሱ ነውና ደስ የሚለው እርሱ ሁሌም ቢሆን በኃጢኣት እስራት ውስጥ ያሉትን ሰዎች መፈለጉ ነው፡፡ አዳምና ሔዋን ከገነት የወጡት ሁለቱን ነገር እውቀትንና ጥበብን በማጣታቸው ነበር፡፡ ይህ ሲባል ግን እግዚአብሔር የሰጣቸውን እርሱን የሚያውቁበትን እውቀት ሰይጣን በሽንገላ ስለወሰደባቸው ነው፡፡ እግዚአብሔር ምን እንዳላቸው ያውቃሉ እርሱ ካላቸው ይልቅ ግን የሰይጣንን ተልኮልና ሽንገላ ሰሙ፡፡ በመሆኑም እነርሱ ፍጡራን እግዚአብሔር ፈጣሪ እንደሆነ የሚያውቁበት እውቀት ከእነርሱ በሸንገላ ሲወሰድ ያኔ ከበለስ ሥር ክብራቸውን አጡ፡፡ ለዚህም ነበር ሁለቱ በአዳም ውስጥ የነበሩት ነገር ግን የጠፉበት እውቀትና ጥበብ ወደታሰሩት ሰዎች የተላኩ፡፡ እነኝህ እውቀትና ጥበብ ለእግዚአብሐር እንድንገዛ የሚያደርጉ ናቸው፡፡ ዕውቀትም ጥበብም እግዚአብሔርን መፍራት ስለሆኑ ነው፡፡ አንድ ሰው እውቀት አለው ተብሎ እንዲሁም ጥበበኛ ነው ተበሎ ለእግዚአብሔር እንደ እግዚአብሔርነቱ ካልተገዛ እውቀቱም ሆነ ጥበቡ ብላሽ ነው፡፡ እግዚአብሔር ለሁሉም ሰው ከሆነ፤ በመስቀል ላይ ከተሰቀለ፤ ሁለቱ ደቀ መዛሙርት እንዲሁ ወደዓለም ከተላኩ ዛሬም ይህ ተዘንግቶ በዘር፤ በጎሳ የሚለያይ ከሆነ የዚህ ሰው እውቀት እንዲሁም ጥበብ እውቀትና ጥበብ መባሉ ቀርቶ ድንቁርናና ብልሹነት ቢባል ይቀላል፡፡ ወደ እግዚአብሔር የሚያደርስ እውቀትም ይሁን ጥበብ የለውምና፡፡ እግዚአብሔርን የምናውቅበት እውቀትና ጥበብ ለቅድስና፤ ለትህትና ያበቃልና ከዚያም ለእርሱ ማደሪያ ወደ መሆን ያደርሳል፡፡ በዛሬውም ወንጌል የምንመለከተው ይህን ነው፡፡ ሁለቱ ደቀ መዛሙርት የተባሉት እውቀትና ጥበብ ወደ ዓለም ሲገቡ ሁሉም ሰው ራሱን ለእግዚአብሔር ማደሪያነት ዝግጁ ያደርጋል፡፡ ሁለቱ የታሰሩት አህያና ውርንጫይቱ ሁለቱ ደቀ መዛሙርቱ ተልከው ካስፈቷቸው በኋላ ልብስ አለበሷቸው ከዚያም ለጌታቸው መቀመጫነት ብቁ ሆኑ፡፡ በጥበብና በእውቀት የተገነባ ሰው ልብስ ለተባለው ቅድስና ሕይወት ብቁ ይሆናል፡- ራእይ፣7፤9 ከዚህ በኋላ አየሁ፥ እነሆም፥ አንድ እንኳ ሊቆጥራቸው የማይችል ከሕዝብና ከነገድ ከወገንም ከቋንቋም ሁሉ እጅግ ብዙ ሰዎች ነበሩ፤ ነጭ ልብስም ለብሰው የዘንባባንም ዝንጣፊዎች በእጆቻቸው ይዘው በዙፋኑና በበጉ ፊት ቆሙ፤ በታላቅም ድምፅ እየጮሁ። በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለአምላካችንና ለበጉ ማዳን ነው አሉ መላእክቱም ሁሉ በዙፋኑና በሽማግሌዎቹ በአራቱም እንስሶቹ ዙሪያ ቆመው ነበር፤ በዙፋኑም ፊት በግምባራቸው ተደፉ፥ ለእግዚአብሔርም እየሰገዱ። አሜን፥ በረከትና ክብር ጥበብም ምስጋናም ውዳሴም ኃይልም ብርታትም ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ለአምላካችን ይሁን፤ አሜን አሉ። ከሽማግሌዎቹም አንዱ ተመልሶ፦ እነዚህ ነጩን ልብስ የለበሱ እነማን ናቸው? ከወዴትስ መጡ? አለኝ። እኔም። ጌታ ሆይ፥ አንተ ታውቃለህ አልሁት። አለኝም። እነዚህ ከታላቁ መከራ የመጡ ናቸው፥ ልብሳቸውንም አጥበው በበጉ ደም አነጹ። ስለዚህ በእግዚአብሔር ዙፋን ፊት አሉ፥ ሌሊትና ቀንም በመቅደሱ ያመልኩታል፥ በዙፋኑም ላይ የተቀመጠው በእነርሱ ላይ ያድርባቸዋል። እንዲህ ባለ ሕይወት ሰው ብቁ ሲሆን ያኔ እግዚአብሔር በእርሱ ላይ ለማደር ይፈልጋል፡፡ ምክንያቱም የቅድስናን ልብስ ተጎናጽፏልና፡፡ ከዚህ በኋላም እግዚአብሔር ባከበረው ሕይወት ውስጥ የሚነጠፈው የክብር ምንጣፍ ብዙ ነው ያውም ሞት ሊይዘው የማይችል፡፡ ቅዱሳን ዛሬም የምናከብራቸው በሚያልፈው ዓለም ውስጥ የማያልፍ ሥራ ሰርተው ስላለፉ ነው፡፡ በአጠቃላይ ልብሶቹ እውነት፤ ቅድስና፤ትዕግሥት፤ ሃይማኖት ናቸው፡፡ እነኚህ ሁሉ ካሉ እግዚአብሔር ሁሌም ከእኛ ሕይወት ውስጥ ይኖራል፡፡
ይቆየን
